‹‹ብ.አ.ዴ.ን.›› የማን ወኪል ነው? ጌታቸው ሺፈራው


መረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ


በአገራችን በስፋት ከሚተረክላቸው ፓርቲዎች መካከል ኢህአፓ ግንባር ቀደሙ ነው፡፡ ይሁንና ‹‹ያ ትውልድ›› ተብሎ የሚነገርለትን ያህል ሳያበረክት በአጭሩ ተቀጭቷል፡፡ ለዚህም በዋነኝነት ከሚነሱት ምክንያቶች መካከል አንዱ በፓርቲው ውስጥ የተነሳው ‹‹አንጀኝነት›› ነው፡፡ በፓርቲው ‹‹የአንጃ›› ታሪክ በነ ብርሃነ መስቀል ረዳና ጌታቸው ማሩ የሚመራው ቡድን የመጀመሪያው ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ ከዚህ ቀጥሎ ደግሞ አሲምባ ላይ ‹‹በዳግማዊ አንጃነት›› የተረሸኑት ይገኙበታል፡፡ ብ.አ.ዴ.ን. ቀደም የነበሩትን ‹‹አንጀኞች›› በማድነቅ ራሱን ‹‹ሳልሳዊ አንጀኛ›› አድርጎ ይቆጥራል፡፡

ምንም እንኳ ብአዴን የኢህአፓን ታሪክ በታሪክነት ቢወስድም ከኢህአፓ ከወጣ በኋላ በተሸከማቸው አብዛኛዎቹ አቋሞቹ ግን አብሮት የነበረ አይመስልም፡፡ አባል የነበረበትን ኢህአፓን የሚያወግዘው ብአዴን/ኢህዴን በተቃራኒው የኢህአፓ ተቀናቃኝ የነበሩትን ህወሓትና ሻዕቢያ ላይ ምንም አይነት ትችት አያነሳም፡፡ እንዲያውም ህወሓትና ሻዕቢያ የተከተሉት መንገድ ‹‹ዴሞክራሲያዊና ትክክለኛ መንገድ ነው›› ብሎ በአድንቆት ተቀብሏቸዋል፡፡ ይህም ኢህዴን/ብአዴንን የኢህአፓ አንድ አካል ሳይሆን ለሌላ ተልዕኮ አብሮ የቆየ እንደሆነ ጥርጣሬ ያጭራል፡፡

ብአዴንና ኢህአፓ

ብአዴን ኢህአፓ ውስጥ የተፈጠረውን ‹‹አንጃ›› አድንቆ ‹‹ሳልሳዊ›› መሆኑን ቢገልጽም አንጃ ከሚባሉትም ጋር ተመሳሳይ መርህ ሲከተል አይስተዋል፡፡ ኢህአፓ ውስጥ ‹‹በአንጃዎቹ›› ከተነሱት አምስት የሀሳብ ልዩነቶች መካከል ሁለቱን ብቻ ብናይ እንኳ ኢህዴን የሚያምንባቸው አይደሉም፡፡ ‹‹አንጀኖቹ›› ካነሱት ሀሳም መካከል አንደኛው ከደርግ ጋር ጸረ ኢድሃና ጸረ ሶማሊያ ግንባር መፍጠር አለብን የሚል ነው፡፡ ሆኖም ኢህዴንን ያቋቋመው ህወሓት ሶማሊያን እስከ ድሬዳዋ በመምራት ቀዳሚው ድርጅት ነው፡፡ ይህን የህወሓት ድርጊት ኢህዴን አንድም ቀን ተችቶ አያውቅም፡፡ በመሆኑም ኢህዴን ከኢህአፓ ነበረኝ የሚለውን ልዩነትና ከህወሓት ጋር ያለውን ግንኙነት ምክንያታዊ ለማድረግ እንጅ ‹‹አንጃዎች›› ያነሱት ‹‹የጸረ ሶማሊያ ግንባር›› ሀሳብ እንደማይስማማ ለመገመት አያዳግትም፡፡
ሌላኛው ‹‹የአንጀኞች›› ሀሳብ ‹‹በ3ኛው ዓለም ፋሽዝም ሊነሳ አይችልም የደርግ ተፈጥሮም ፋሽዝም አይደለም›› የሚል ነበር፡፡ ምንም እንኳ ብአዴን ‹‹ከአንጀኖቹ›› አንድ አካል መሆኑን ቢገልጽም የኢህዴንን ታሪክ የተረከባት ‹‹ፅናት›› መጽሃፉ አብዛኛው ክፍሏ የደርግን ‹‹ፋሽስትነት›› ነው የምታወራው፡፡ የመጽሃፏ ርዕስ እንኳ ‹‹ከፋሽስታዊ ጭፍጨፋና አፈና ያልተነበረከከው …የተጋድሎ ታሪክ›› የሚል ነው፡፡ ብአዴን በመጽሃፉ ‹‹የኢህአፓ አመራር ግን እነዚህን አብይ ጥያቄዎች ተገቢውን ውይይት ተደርጎባቸው አባላቱ እንዲረኩ የድርጅቱ ዴሞክራሲያዊነትም እንዲረጋገጥ ለማድረግ ፍላጎት አልነበረውም፡፡››(22) ቢልም እሱ ከ‹‹አንጃውም›› ሆነ ከዋናው ኢህአፓ ጋር ይህ ነው የሚባል ተመሳሳይ አቋም እንዳልነበረው ለመገንዘብ ይቻላል፡፡
ከኢህአፓም ይሁን ‹‹አንጀኖቹ›› ይልቅ ብአዴኖች ቀድሞውንም ለህወሓት ልባዊ ፍቅር እንደነበራቸው ራሳቸው ያሰፈሩት ታሪክ ይናገራል፡፡ የብአዴን መስራቾች ከኢህአፓ ጋር በይፋ የተለያዩት ህወሓት ላይ ምላጭ አንስብም ብለው ነው፡፡ ሆድ ያባውን እንዲሉ ውስጥ ለውስጥ የነበራቸውን ፍቅር ኢህአፓ ከህወሓት ጋር ውጊያ በገጠመበት ወቅት በህወሓት ላይ ምላጭ መሳብ የሚችል ‹‹ጨካኝ›› ልብ እንደሌላቸው አስመስክረዋል፡፡ ‹‹በ1972 ዓ/ም ወደ ወልቃይት ተጠርተው ሄደው የነበሩት ሁለት የበለሳ ሀይሎች ወልቃይት ላይ በተደረገው የኢህአፓና የህወሓት ጦርነት ላይ እንዲሳተፉ ትዕዛዝ ተሰጥቷቸው እንዷ ሀይል አሻፈረኝ ብላ ወደ በለሳ ስትመለስ ሌላዋ ሀይል በጉዳዩ ላይ ባደረገችው ውይይት በመሃሏ ልዩነት ስለተነሳ ከሁለት ተከፍላ ከነበራት 55 አባላት 22ቱ ከሀይሏ ተገንጥለው ወደ በለሳ ተመልሰዋል፡፡ ይህች ጋንታ በበለሳ ዴሞክታሲያዊ ንቅናቄ ታሪክ ውስጥ ጋናታ 22 ተብላ ትጠራለች››(85)፡፡ የብአዴን መስራቾች የኢህአፓ አካል የነበሩት ሁለቱም ‹‹አንጃዎች›› ሲመቱ ምንም ሳይሉ ህወሓት ጋር ጦርነት ሲጀመር ልዩነታቸውን መፈንዳቱ የቆየ ልባዊ ግንኙነት አሊያም ተልዕኮ ካልሆነ በስተቀር አጋጣሚ ሊሆን አይችልም፡፡ ከዚያ በፊትም በበለሳ፣ ወልቃይትና የትግራይ ከተሞች በርካታ አመራሩ እንጅ ተዋጊው የማያምንባቸው ውጊያዎች ቢካሄዱም የብአዴን መስራቾች ግን ያንገበገባቸው ከህወሓት ጋር የነበረው ጦርነት ነው፡፡
ከጦርነት ባሻገር ኢህአፓ ውስጥ የነበራቸውን አቋም በአንዴ አሽቀንጥረው ከህወሓት አቋም ጋር መላመድ ያልከበዳቸው መሆኑ ደግሞ ኢህአፓ ውስጥ የነበሩ ‹‹ህወሓቶች›› ስለመሆናቸው ጥርጣሬን ያጭራል፡፡ በኢህዴኗ መጽሃፍ ‹‹ከህወሓት ጋር የነበረውን ግንኙነት ጠቅሶ ከህወሓት ጋር ግንባር መፍጠር ይቻል እንደነበር አስምሮበታል፡፡ በአጠቃላይ የብሄር ጥያቄ በኢትዮጵያ ያለውን ቦታ ሲመለከትም ህወሓት አንግባው የተነሳችው ጥያቄ ዴሞክራሲ ጥያቄ መሆኑን አስተውሏል፡፡›› ሲሉ ከኢህአፓ ይልቅ ድሮም ለህወሓት ቅርብ እንደነበሩ ያስረግጥልናል፡፡ ኢህአፓና ህወሓት ሲቃቃሩ የብአዴን መስራቾች ‹‹ከኢህአፓ ተገንጥለው ሳይውሉ ሳያድሩ ከሚያዚያ ጀምሮ በወሎ ክፍለ ሀገር በዋግ አውራጃ ውስጥ ህዝባዊ ሰራዊቱን አስገብተው ትጥቅ ትግሉን በአዲስ መሰረት ላይ ጣሉ›› (ፅናት፣ 117)፡፡ ከኢህአፓ ከወጡ በኋላ አዲሱ ተግባራቸውን በትዕዛዝ የጀመሩት ይህኔ መሆኑ ይነገራል፡፡ ኢህአፓ ከሚታወስባቸው ጉዳዮች መካከል ብአዴኖች ‹‹ፅናት›› ባሏት መጽሃፍ መግቢያ ላይ
‹‹ፍጹም ነው እምነቴ
የትግሉ ነው ህይወቴ
ልጓዝ በድል ጎዳና
በተሰውት ጀግኖች ፋና›› በሚል ያስቀመጡት መዝሙር ተጠቃሽ ነው፡፡
ኢህአፓ ‹‹ጽኑ ነው እምነቴ›› ሲል ህወሓት ለተነሳለት የከፋፍለህ ግዛ ስርዓት ሳይሆን ለህብረ ብሄርተኝነት እንደነበር ይታወቃል፡፡ ይሁንና ብአዴን መዝሙሩን እየዘመረም ቢሆን ጽናት እንደሌለው የህወሓትን ፖሊሲዎች ትክክለኛ እንደሆኑ ይገልጽልናል፡፡ ‹‹በኢህአፓ ምክንያት በጭቁን ህዝቦችና በታጋይ ድርጅቶች መካከል ሊኖር የሚገባውን ህብረት ለመፍጠርም ከፍተኛ ትግል አድርጓል፡፡ ኢህአፓ ወላዋይና ትምክተኛ ድርጅት ስለነበረ ያደናቀፈውን የጭቁኖች አንድነት በጠንካራ መሰረት ላይ እንዳለ ለመገንባት ከህወሓት ጋር በጋራ ባደረገው ትግልም አኩሪ ድሎችን አስመዝግቧል››(139)፡፡ ብሎ ህወሓት ከእነ ምናምኑ ይቀበለዋል፡፡ ይህ እንግዲህ የብአዴን መስራቾች ከኢህአፓ ለመውጣት ያነሷቸው ከነበሩት መከራከሪያዎች መካከል ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ በወቅቱ ኢህአፓን ‹‹ትምክተኛ፣ ግትር፣…›› እያሉ የሚወቅሱትም ሆነ ህወሓትን የሚያወድሱበት ‹‹ጽኑ ነው እምነቴ›› ከሚለው ኢህአፓ ይልቅ የህወሓትን ቋንቋ ተውሰው ነው፡፡

ብአዴንና ህወሓት

ከኢህአፓ ይልቅ ለህወሓት መልካም አመለካከት የነበረው ‹‹ንቅናቄው›› ከኢህአፓ ተነጥሎ የህወሓትን ድጋፍ ለማግኘት ጊዜ አልወሰደበትም፡፡ ‹‹ህወሓት ለመደራጀት በምናደርገው ጥረት ልትተባበረን ትችል ይሆናል፣ ይህ ካልሆነም በመስዋትነት የተገኘው ንብረታችንን ለደርግ ከመስጠት ለህወሓት መስጠት ተገቢ ይሆናል፡፡›› የሚል ስምምነት ላይ ደረሱ፡፡ በአሁኑ ወቅት ብአዴን ስልጣንም ሆነ በሌሎች ጉዳዮች አሳልፎ መስጠትና ህወሓት ያለውን ማስፈጸም በግልጽ የጀመረው በዚህ ወቅት ይመስላል፡፡ በስንክሳራቸው ስላልገለጹትና ህወሓትም ከእሱ ጋር ከሚሆኑ ይልቅ አዲስ መሸጋገሪያ ድርጅት ቢፈጥሩ ይበልጥ እንደሚጠቀም ስላሰበ ይሆናል እንጅ እንደዚህ ፍቅራቸው የህወሓት አንድ አካል ለመሆን ጥያቄ አንስተው ሊሆን እንደሚችል መገመት አያዳግትም፡፡
ሰኔ 20 1972 ንቅናቄው ከህወሓት ጋር ግንኙነት ካደረገ በኋላ (ከዛ በፊት መሰረታዊ ግንኙነት እንዳላቸው የሚጠረጥሩበት በርካቶች ናቸው) በህወሓት የሀሳብ መሪነት አዲሱ የድርጅት ጉዞውን ቀጠለ፡፡ በእነዚህ ጊዜያት የህወሓት መሪዎች ትልቁን ሚና ተጫውተዋል፡፡ በአሁ ወቅት ህወሓት/ኢህአዴግ በአጋር ፓርቲዎች አማካሪም ሆነ እሱ ብቻ የመከረበትን ሀሳብ የሚጭንበት ታሪክም የጀመረው በዚሁ የኢህአፓው ተገንጣይ ቡድን ላይ ነው፡፡ ህዳር 11 1972 ዓ/ም ትግራይ ውስጥ በተምቤን አውራጃ አምባራ ወረዳ ሽልምዕምኒ ቀበሌ ተክራርዋ በተባለ መንደር መስራች ጉባኤው ተቋቋመ፡፡ በዚህ ወቅትም መግባባት የተደረሰበት የድርጅቱ ዋነኛ መስመር ‹‹አብዮታዊ ዴሞክራሲ›› እንዲሆን ነው፡፡ ‹‹ከሰኔ 20 ቀን 1972 እስከ ህዳር 7 1973 ለ5 ወራት የተካሄደው ዝግጅት መካከል አንዱ የኢህአፓን የተሳሳተ መስመር በመሻር አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ አቋሞችን የመውሰድ ዝግጅት ማድረግ ነው፡፡›› (ፅናት፤ 99)፡፡ እንግዲህ የብአዴን መስራቾች ለበርካታ ጊዜ አብረውት ኖረው ‹‹የተሳሳተ›› ከሚሉት የኢህአፓ መንገድ ይልቅ አሁን አርሶ አደሩን ጭምር የሚያደርቁበት የህወሓት ‹‹አብዮታዊ ዴሞክራሲ›› እንዲሁ የተቀበሉት በተንበኗ ትንሽ መንደር በተገናኙባት ጥቂት ቀናት ውስጥ መሆኑ ነው፡፡
ህዳር 11 1972 ተከራዋ ከተባለችው መንደር ውስጥ ኢህዴን ተመሰረተ፡፡ ብአዴን በዚች መንደር የተመሰረተበትን 35ተኛ አመቱን አክብሯል፡፡ የአሁኑ ብአዴን ራሱን ኢህዴን ብሎ ይቆይ እንጅ የህወሓትን መስመር ሳያንገራግር የተቀበለው የምስረታው ጊዜ ነው፡፡ ተከራዋ በተባለችው መንደር ኢህዴን ከህወሓት የተቀበለው አብዮታዊ ዴሞክራሲን ብቻ አልነበረም፡፡ ይልቁንስ ኢህአፓ የሚቃወመውን የኤርትራን የመገንጠል መብትም ተቀብሎ ተመለሰ፡፡ ይሁንና ወደ ወሎና በለሳ ተመልሶ በዚህ ፖሊሲው ከህዝብ ጋር መግባባት እንደማይችል በመታወቁ መለስተኛ ለውጥ እንዲደረግበት ተወሰነ፡፡ በመሆኑም ‹‹የኤርትራ ህዝቦችን የራስን እድል በራስ የመወሰን መብት እስከ መገንጠል መብት ያከብራል›› የሚለውን መጀመሪያ ላይ ሳያንገራግር የተቀበለውን መርህ ‹‹የኤርትራ ህዝቦችን የራስን እድል በራስ የመወሰን መብት እስከ ነጻነት ያውቃል›› በሚል ግራ አጋቢና ጊዜያዊ አቋም ተክቶ ወደ ስራ ገባ፡፡ በእርግጠኝነት ይህኛውንም ቢሆን ህወሓትን ፈቃድ ውጭ ሊቀየር የሚችል አልነበረም፡፡ ይህን አቋም ስልጣን ሊይዙ በተቃረቡበት ወቅት እንደገና እንዲቀይር ተደርጓል፡፡ ህብረ ብሄራዊነት፣ ከዛም ‹‹አማራን›› የወከለ የሚያስመስለው ስምም ህወሓት አባይን ለመሻገር በሚጠቅም መልኩ የቀረጸው እንደነበር የሚያጠራጥር አይደለም፡፡

ብአዴንና አማራ

ኢህዴን ከተመሰረተ በኋላ አብዛኛዎቹ መስራቾች ከህወሓት ጋር ያለውን ግንኙነትም ሆነ አዲሱን ፖሊሲውን ተቃውሞው ጥለው ወጥተዋል፡፡ ለአብነት ያህል በመስራች ጉባኤው ከተመረጡት 9 አባላት መካከል የቀሩት አምስቱ ብቻ ነበሩ፡፡ ሌሎቹ ከህወሓት ጋር ባለው ግንኙነትም ሆነ በአዲሱ አቋም ባለማመናቸው ከትግሉ ወጥተዋል፡፡ ያም ሆኖ ኢህአዴን በህብረ ብሄርነት ስም ለ9 አመታት ሲንቀሳቀስ ቆይቷል፡፡ ስልጣን ለመያዝ በተቃረበበት ወቅት ግን ‹‹አማራን›› የወከለ የሚያስመስል ስም ለጥፎ ወደ መሃል አገር ህወሓትን መምራቱን ተያያዘው፡፡

ኢህዴን (ብአዴን) ከህወሓት በሚደረግለት ድጋፍና ትዕዛዝ ዋነኛ መንቀሳቀሻው ወሎና ጎንደርን አድርጎል፡፡ በዚህ ወቅት በእነዚህ አካባቢዎች ህዝቡ በርካታ ችግሮች ተጋፍጦ ከጎኑ ተሰልፎ ተዋግቷል፡፡ ሆኖም ብአዴን ህወሓትን ቤተ መንግስት ካደረሰ በኋላ አብሮት የተዋደቀውን ህዝብ ተመልሶ አላየውም፡፡ ሌላው ይቅርና ከህወሓት ጋር አንዋጋም ብለው ከኢህአፓ ከወጡት ውጭ ህዝብ ላይ የደረሰውን በደል ተነግሮ አያውቅም፡፡ ለአብነት ያህል የሀሙሲትን ጭፍጨፋ ማንሳት ይቻላል፡፡ ኢህዴን/ብአዴን ይንቀሳቀስባቸው ከነበሩት ከተሞች አንዷ የሆነችው ሀሙሲት ከሀውዜን ባልተናነሰ በደርግ አውሮፕላኖች የወደመች ከተማ ነች፡፡ በገበያ ቀን በተደረገው ድብደባ ሰውም ሆነ እንሰሳ አልተመለሱም፡፡ ሆኖም ስለዚች ከተማ ሲወራላት ተሰምቶ አይታወቅም፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የብአዴንና የህወሓት ታጋዮች ህዝቡ በደርግ ላይ እምነት እንዲያጣ ቤተ ክርስቲያንን ጨምሮ እንደ ትምህርት ቤት ያሉ የህዝብ መገልገያዎች ላይ በመጠለል አሊያም እንደተጠለሉ በማስወራት በርካታ ተቋማት በደርግ እንዲወድሙ አድርገዋል፡፡ ይህ በሆነበት ግን ህወሓት በአካባቢው የነበሩትን ሀብቶች ማጓጓዙን ተከትሎ ጥያቄ ሲያነሳ ከብአዴኖች የሚሰጠው መልስ ‹‹እናንተ ምን ደረሰባችሁ?›› የሚል ነው፡፡ ለምሳሌ ያህል ከአስር አመት በፊት ጎንደር ተማሪዎች ከተማው ውስጥ የነበረን አንድ ዘመናዊ ጀኔሬተር በህወሓት መወሰዱን ተከትሎ ባነሱት ጥያቄ ከብአዴን የተሰጠው መልስ ‹‹የተደበደቡት፣ የቆሰሉት፣ የተዋጉት፣ የተጨፈጨፉት›› እነሱው ናቸው የሚል ነው፡፡ ብአዴን እንዱ ህዝብ ለሌላኛው የጦርነት ካሳ መክፈል እንዳለበት ለማሳመን የሚያደርገው ጥረት ህዝብ ከህዝብ ጋር ለማናቆር ሆን ተብሎ የተዘየደ ስልት ነው፡፡ በምሳሌነት የምትነሳው ደግሞ ሀውዜን ነች፡፡ የሀውዜን መደብደብ ዋነኛው ተዋናኝ ህወሓት እንደነበር የቡድኑ ታጋዮች እማኝነታቸውን ሰጥተዋል፡፡ የሀሙሲት ጉዳይም አንድ ቀን ታሪክ የሚያወጣው ይሆናል፡፡

የወሎና የጎንደር ህዝብ ከጎኑ ሆኖ እንደታገለ ብአዴን ራሱ አይክድም፡፡ ይሁንና ከስም ያለፈ ተግባራዊ ውክል ኖሮት አያውቅም፡፡ ከኢህአዴግ ጎን ተሰልፈው የተዋጉ አርርሶ አደሮች የሚገባውን እንዳላገኘ በምሬት ሲገልጹ ኢቲቪና ኢህአዴግ አቶ መለስን ‹‹የህዝብ ልጅ›› ለማስመሰል ባቀረበው ዶክመንተሪ ላይ ታይቷል፡፡ ይህ ጸሃፊ በተገኘበት አንድ መድረክ ከኢህዴን ጎን ቆመው የታገሉ አርሶ አደሮች አዲሱ ለገሰን ከድተኸናል በሚል በዚህ ጽሁፍ ሊገለጽ የማይችልን ስድብ ሲያወርዱበት ታዝቧል፡፡ ስድብና ወቀሳ የበዛበት አዲሱ ለገሰ በሌላ ወቅት የአርሶ አደሮቹን ቁጣ ያበርዳል የተባለ መለስተኛ የመስኖ ፕሮጀክት ለማስመረቅ ወደ አካባቢው በሄደበት ጊዜ ህዝቡ መንገዱን ዘግቶ አላሳልፍም በማለቱ ሄሊኮፍተር ከባህርዳር መጥቶለት ሲመለስ ምስራቅ መኮነን አዲሱ ወደ ባህርዳር መመለሱን በመግለጽ ህዝቡን ‹‹አረጋግታ›› እንድትመልስ ተደርጓል፡፡ በአሁኑ ወቅት የአካባቢው ህዝብ ለብአዴን ያለው አመለካከት ጭራሹን የወረደ ነው፡፡
በእርግጥ ብአዴን በአርሶ አደሩ ብቻ ሳይሆን አብረውት ወደ ቤተ መንግስት ለገቡት ተዋጊዎችም እንዳልሆነ ተስፋዬ ገብረ አብ አስነብቦናል፡፡ ተስፋዬ ‹‹የጋዜጠኛው ማስታወሻ›› በተሰኘው መጽሃፉ ተፈራ ዋልዋ ‹‹እኛ ኢህዴኖች ውጊያ ላይ ወደ ኋላ በማፈግፈግ መሳሪያ ሲከፋፈል ደግሞ በመንጫጫት እንታወቃለን፡፡ በውጊያ ወቅት ‹‹ህወሓት ይዋጋ እንደ ጦጣ በቆንጥርና በተራራ መሮጥ የለመዱት እነሱ ናቸው ትሉ አልነበርም? ህወሓት ተሰውቶ የያዘውንና የማረከውን መሳሪያ ደግሞ ካልተካፈልን እያላችሁ ታጉረመርሙ አልነበረም? ስለ ስልጣን ከማውራታችሁ በፊት እስኪ ስንቶቻችሁ ናችሁ የተሰጣችሁን ስራ አድምታችሁ የሰራችሁ!?›› በሚል ዳግመኛ ለህወሓት ቆሟል፡፡ ከዚህ የምንረዳው ብአዴን ያኔ ኢህአፓ ከተገነጠለበት ጊዜ ጀምሮ ከህወሓት የተዋሰውን ቋንቋ ስልጣን ይዞም በስፋት እየተገበረው መሆኑን ነው፡፡ ለህወሓቶች ቆሞ የነበረው ተፈራ ዋልዋ እነ ስብሃት ነጋ ፖለቲካውን በሚያሾሩበት ወቅት አድራጊ ፈጣሪው ህወሓት ‹‹መተካካት›› ብሎ ባመጣው ፖሊሲ ከመድረኩ አርቆታል፡፡
ሻምበል አስረስ የተባለ የብአዴን ካድሬ ‹‹የደራሲው ማስታወሻ›› በተሰኘ መጽሃፉ ደግሞ ህወሓትና ሻዕቢያ ብአዴን ወክየዋለሁ የሚለውን ህዝብ በማን አለብኝነት ሲጨፈጭፉ ምንም ማድረግ አለመቻሉን ይነግረናል፡፡ ካድሬው በ1987 ዓ/ም ለስራ ወደ አዘዞ በሄደበት ወቅት ምሽት ላይ ከፍተኛ ጮኸት ይሰማና ከአንድ ሌላ የህወሓት አባል ጋር ጩኸት ወደተሰማበት ቦታ ያቀናሉ፡፡ በቦታው በደረሱበት ወቅት ያዩት ጉዳይ ግን ለማመን የሚከብድ ነበር፡፡ ‹‹አዘዞ በሚገኘው ወታደራዊ ካምፕ ውስጥ ፈንጠር ብለው (ለድብደባ) የተሰሩ ቤቶች የታጠቁ የደህንነት ሀይሎች እጃቸው የታሰሩ ሰዎችን መሬት ላይ አጋድመው በአጣና ጉማጅ አናት አናታቸውን ልክ እንደ እባብ ይቀጠቅጧቸዋል፡፡ ግማሾቹ በደም ተነክረው ተዘርረው ያቃስታሉ፡፡ አንዳንዶቹ ሰቅጣጭ ጩኸት ያሰማሉ፡፡ ሌሎቹ ስቃይ የበዛባቸው ትንፋሻቸው እንኪቆራረጥ በከፍተኛ ድምጽ የድረሱልኝ ጮኸታቸውን ይለቁታል›› (178፣ 179)፡፡ ሻምበሉ አጣርቼ አገኘሁት እንደሚለው በአሰቃቂ ሁኔታ ጭፍጨፋ የተፈጸመባቸውም በጎንደር ከተማና አካባቢው ህወሓትና ሻቢያ ‹‹ነፍጠኛ›› ብለው የፈረጇቸው ግለሰቦች ናቸው፡፡ የሚገርመው ደግሞ በአሰቃቂ ሁኔታ ሰዎችን እንዲህ በአጠና በአሰቃቂ ሁኔታ የሚደበድቡት የህወሓት አባላት ብቻ አለመሆናቸው ነው፡፡ ኢህዴን አንድ ግዜ ‹‹የመገንጠል መብታቸውን እናውቃለን፣ ሌላ ጊዜ እናውቀላን፣ እናደንቃለን›› ይልላቸው የነበሩት የሻዕቢያ ካድሬዎች ጭምር እንጅ፡፡

የብአዴን ካድሬ የነበረው ሻምበል አስረስ ህወሓት በፈለገው ጊዜ ብአዴን አስተዳድረዋለሁ ከሚለው አካባቢ የሚወስዳቸውን አካባቢዎች እንደፈለገ መከለል የጀመረው ከ23 አመት በፊት መሆኑንም ያስረዳል፡፡ ሻምበሉ ሱዳን ለሚገኙ ኢትዮጵያውያን ኢህአዴግ ስለሚመሰርተው ‹‹የድሮው አስተዳደር በወንዝና በተራራን መሰረት አድርጎ የተከለለና ፍትሃዊ ያልበረ በመሆኑ አዲሱ የህዝብ ለህዝብ አንድነትን ለማምጣት የሚያስችል እንደሆነ እንዲቀሰቅሱ መመሪያ ይሰጣቸውና ቅስቀሳ ይጀምራሉ፡፡ ይሁንና የካድሬ (ክፍለ ህዝብ) መሪ የነበረው የህወሓት ካድሬ አንድ ቦታ ላይ ‹‹(ህወሓት) በፊውዳሉ በተለይም በአጼ ኃ/ስላሴ ዘመን መንግስት የትግራይ ህዝብ የተቀማውን መሬት ማለትም አላማጣን፣ ኮረምን፣ ሁመራንና ወልቃይትንና የመሳሰሉ መሬቶችን አስመልሷል፡፡ ወደፊትም እየተጠና የምናስመልሰው ይኖረናል›› በሚል ህዝብን ለመያዝ በመመሪያ የተሰጣቸውን ሳይሆን የህወሓትን ዋነኛ አላማን ለህዝብ ያቀርባል፡፡ በዚህ አጋጣሚ ህዝብ ግራ ለመጋባትም አልፎ ቁጣ ይቀሰቀሳል፡፡ በካድሬዎቹ መካከል አለመግባባት ተፈጥሮም እርስ በእርሳቸው ተደባድበዋል፡፡ ሆኖም ከ‹‹መርህ›› ውጭ የቀሰቀሰው የህወሓት ካድሬ እርምጃ ይወሰድበታል ሲባል የብአዴኑ ሻምበል አስረስ ስራ እንዲያቆም ተደርጓል፡፡ ያ የህወሓት ካድሬ ‹‹ወደፊትም እየተጠና የምናስመልሰው ይኖረናል›› ያለው አሁንም እውን እየሆነ ይመስላል፡፡ በቅርቡ ከጎንደር አካባቢ የተከለሉ ሁለት ወረዳዎች እንዳሉ መገለጹ ይታወቃል፡፡ (ብአዴን አስተዳድረዋለሁ የሚለው መሬት ለሱዳንም ይሁን ለህወሓት ካድሬዎች እንዲከፋፈል በደስታ ፈርመው እያስረከቡ ነው የሚባሉት ም/ጠ ሚኒስተር ደመቀ መኮነንንና፣ የክልሉ ምክትል አስተዳደር ገዱ አንዳርጋቸውን የመሳሰሉት በርካታ የብአዴን አመራሮች ‹‹እናስተዳድረዋለን›› በሚሉት ህዝብ ዘንድ የተጠሉ መሆናቸው ይታወቃል፡፡) እንግዲህ ፌደራል ስርዓቱ ከተመሰረተ ከ23 አመት በኋላ እንደገና ክለላ፣ እንደገና የመሬት ወረራ ‹‹ብአዴን›› የህወሓት አካልና አገልጋይ እንጅ አንድ ራሱን የቻለ ፓርቲ አለመሆኑን የሚያሳይ ነው፡፡ ብአዴን ኢህአዴግ ወደ ስልጣን ሲመጣ ህወሓት ያለውን ተቀብሎ ቀጥሏል፡፡ በ1993ቱ ክፍፍል ደግሞ ከህወሓት የወጡትን ለመተካት በሚመስል መልኩ ለአቶ መለስና ህወሓት ተገን ሆኖ አገልግሏል፡፡ አቶ መለስ ከሞቱ በኋላ የተሰጠውን አስፈጻሚነት ሲቀማም ቢሆን ህወሓትን በማክበር ልምዱ ያለ ማንገራገር ተቀብሎታል፡፡
በ1997 ምርጫ ደግሞ የብአዴን አባላት ‹‹እንወክለዋለን በሉ!›› የተባሉትን ህዝብ በህወሓት ቋንቋ በጅምላ በነፍጠኝነት የከሰሱበት ወቅት ነበር፡፡ ኢህዴን/ብአዴን ‹‹ትግሉ የአማራ ገዥ መደቦች በጭቁን ብሄሮችና በአማራው ህዝብ መካከል ፈጥረውት የነበረውን የእርስ በእስር መጠራጠርና አለመተማመን አስወግዷል›› (ፅናት፣ 139)፡፡ ቢልም ቀድሞውንም ቢሆን በገዥ መደብ መካከል እንጅ በህዝብ መካከል ይህ ነው የሚባል አለመተማመን ነበር ለማለት አይቻልም፡፡ በአሁኑ ወቅት ግን የድሮው ኢህአዴን ወክየዋለሁ የሚለው አማርኛ ተናጋሪ ከህዝብ ሳይሆን ከበርካታ ክልሎች በገዥዎች የማፈናቀል ሰለባ በመሆን ላይ ይገኛል፡፡ ከህወሓት ጋር በመሆን ህዝብን ከህዝብ ጋር ለማስማማት ተነሳሁ የሚለው ብአዴን ጭራሹን በህዝብ መካከል መቃቃርን ፈጥሯል፡፡ ብአዴን አስተዳድረዋለሁ ከሚለው አካባቢ በህወሓት የሚወሰዱ ንብረቶች፣ የሚከለሉ መሬቶችና መቀስቀሻዎቹ ሆን ተብሎ በህዝብ መካከል ያለውን ድልድይ በመስበርና አለመተማመን እንዳይኖር ማድረግ ህወሓት ለብአዴን በአስፈጻሚነት የሰጠው ዋነኛው ‹‹የአብዮታዊ ዴሞክራሲ›› መርህ ይመስላል፡፡
በተለይ በአሁኑ ወቅት ህዝብ በርሃብ እያለቀ ‹‹የአማራ ወኪል›› ነኝ የሚለው ብአዴን እወክለዋለሁ የሚለውን ህዝብ ‹‹የትምክት ልሃጩን ያላራገፈ …..›› እያሉ በሚሰድቡት እነ አለምነው መኮነን አሳላፊነት 35ኛ አመቱን በፌሽታ ሲያከብር ከርሞ፣ በርካታ ገንዘብ የፈሰሰበት ሀውልት ማስመረቁን ስናይም ከህዝብ ይልቅ ለራሱና አላማውን እንዲያስፈፅምለት ላቆመው ወኪል መሆኑን በግልፅ የሚያሳይ ነው፡፡ ለህወሓት!