ከሐዋርድ ዩኒቨርሲቲ የተመለሰው የብራና መጽሐፍ እያወዛገበ ነው


መረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ


ከሐዋርድ ዩኒቨርሲቲ የተመለሰው የብራና መጽሐፍ እያወዛገበ ነው
“እውነት እና አገልግሎት” ተቋማዊ ብሂሉና መፈክሩ ነው፡፡ በተለይ፣ ለጥቁሮች በሚሰጠው የከፍተኛ ትምህርት ዕድልና አስተምሮ በሚያወጣቸው ጥቁር ምሁራን ብዛት ይታወቃል – የአሜሪካው ሐዋርድ ዩኒቨርስቲ፡፡

የዘርና የቀለም ልዩነቶች፣ ፖሊቲካዊና ኢኮኖሚያዊ በደሎች ያስከተሏቸውን መድልዎች፤ ለማኅበራዊ ፍትሕ በቆሙና ለሰብአዊ ነፃነት በሚሟገቱ ምሁራን ማስወገድ ዓላማው ያደረገው ዩኒቨርስቲው፤ በአፍሪካ፣ በአሜሪካና በሌላውም ዓለም የተበተኑ ጥቁሮችን የታሪክና የባህል ቅርሶች ያካበተበት የምርምር ማዕከሉም ከዓለም በቀዳሚነት ከሚጠቀሱት መካከል ያደርገዋል፡፡
በየአጋጣሚው ያሰባሰባቸውን ቅርሶችና ውርሶች፣ ወደ ጥንት ቦታቸውና ትክክለኛ ባለቤቶቻቸው በሕጋዊ መንገድ መመለስ፣ “ታሪካዊና ባህላዊ ሀብቶቹን ማክበር ነው፤” ይላሉ፣ የዩኒቨርስቲው የሥነ መለኰት ት/ቤት የአካዳሚያዊ ጉዳዮች ተባባሪ ዲን ዶ/ር ጌይ ባይረን፡፡ በተለይም ኢትዮጵያዊ ቅርሶችን ለኢትዮጵያ የመመለስ ጉዳይ፣ የት/ቤቱ የቆየ ፍላጎት እንደነበርና ይህም በአሜሪካም ሆነ በሌላው ዓለም ቅርሶቹን በግልና በተቋም ለያዙ ግለሰቦች፣ ሙዝየሞችና ተቋማት አርኣያነት እንዳለውና ተነሣሽነትንም እንደሚፈጥር ዶ/ር ባይረን ያስረዳሉ፡፡

በት/ቤቱ ማኅደረ ቅርስ ከተከማቹት ኢትዮጵያዊ የብራና ሥነ ጽሑፍ ሀብቶች መካከል፣ ገድለ ቅዱስ ሰራባሞንና ገድለ ቅዱስ ጳውሎስ አንዱ ነው፡፡ የብራና መጽሐፉ፣ በ1993 ዓ.ም. ዶ/ር አንድሬ ቲውድ ከተባሉ የዩኒቨርስቲው የቀድሞው ተማሪ በስጦታ የተበረከተ ሲሆን የ4ኛው መ/ክ/ዘመኑን ሰማዕት ቅዱስ ሰራባሞንና የሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስን ገድል በአንድ ጥራዝ የያዘ ነው፡፡ ከግብጽ ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ ከዐረብኛ ወደ ግእዝ የተተረጎመው በዘጠነኛው የደብረ ሊባኖስ ዕጨጌ አባ መርሐ ክርስቶስ አስተዳደር(ከ1456-1490 ዓ.ም.) ነበር፡፡

የጥንተ ክርስትና እና የሐዲስ ኪዳን ምሁር የሆኑት ዶ/ር ባይረን፣ የብራና መጽሐፉን ወደ ዲጅታል በመለወጥ፣ የትመጣውን ለማወቅ ጥናት ካደረጉት የሥነ መለኰት ት/ቤቱ ምሁራን አንዱ እንደነበሩ፣ የዩኒቨርስቲው ድረ ገጽ ዘግቧል፤ የገድሉ ጥንተ ባለቤት የደብረ ሊባኖስ ገዳም መሆኑ የታወቀውና ወደ ጥንት ቦታው ለመመለስ የተወሰነውም በጥናቱ ሒደት እንደነበር በዘገባው ተገልጧል፡፡ ከገድሉ ይዞታ ጋር በተያያዘ አስተዳደራዊና ሕጋዊ አካሔዶችን ጨምሮ የተለያዩ ዕንቅፋቶች ዩኒቨርስቲውን እንዳጋጠሙት፣ ድረ ገጹ በጥናቱ የተሳተፉ ምሁራንን ጠቅሶ ዘግቧል፡፡
ዩኒቨርስቲው ገድሉን ወደ ጥንት ቦታው በሕጋዊ መንገድ ለመመለስ በማሰብ፣ በሕግ አማካሪው አርቃቂነት “የስጦታ ውል” የተሰኘና በስምንት ነጥቦች የተዘረዘረ የስምምነት ሰነድ አዘጋጅቷል፡፡ ውሉ በሐዋርድ ዩኒቨርስቲና በደብረ ሊባኖስ ገዳም መካከል የተፈፀመ መሆኑን የሚገልፀው ዘገባው፤ በሥነ መለኰት ት/ቤቱ ዋና ዲን ዶ/ር አልቶን ፖላርድና በገዳሙ ፀባቴ (አስተዳዳሪ) አባ ወልደ ማርያም አድማሱ እንደተፈረመበትም ጠቁሟል፡፡ ይሁንና የውሉ ይዘት  ከባለቤትነት መብትና ከቅርሱ አመላለስ ጋር የተያያዙ ጥያቄዎችን የሚያስነሳ ሆኖ ተገኝቷል ይላሉ ምንጮች፡፡
ዩኒቨርስቲው÷ “ከማናቸውም ግዴታ ነፃ የሆነ የባለቤትነት መብት በብራና መጽሐፉ ላይ አለው” የሚለው የውሉ መግቢያ፣ ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሚመልሰውም “በስጦታ ለመስጠት በመፈለጉ” እንደኾነ ይገልፃል፡፡ የብራና መጽሐፉን ለገዳሙ በስጦታ የሚሰጥበት የባለቤትነት መብት እንዳለው ገዳሙ መስማማቱን የሚገልፀው ውሉ፤ ገዳሙም የብራና መጽሐፉን ሲቀበል፣ ዩኒቨርስቲው ሙሉ በሙሉ የሚያስተላልፈው፣ “አካላዊ የባለቤትነት መብት”ን እንደሆነ አስፍሯል፡፡ ገዳሙን በመወከል የፈረሙት ሓላፊም፤ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የውል ስምምነቱን እንድታከብር የሚያደርግ ዋስትና የመስጠት ሥልጣን እንዳላቸው በውል ሰነዱ ላይ ተመልክቷል፡፡

ባለፈው ሰኞ፣ የዩኒቨርስቲው ሓላፊዎችና ምሁራን በፓትርያርኩ ጽ/ቤት ተገኝተው ገድለ ቅዱስ ሰራባሞን ወጳውሎስን ለገዳሙ ባስረከቡበት ወቅት፣ በግልጽ የተነሡት ተቃውሞዎችና ስጋቶች፣ አስተዳዳሪው ከዩኒቨርስቲው ጋር የተፈራረሙት ሰነድ፣ የገድሉን ባለቤትነት ለገዳሙ ሳይሆን ለዩኒቨርስቲው መስጠቱን አረጋግጧል፡፡

ዩኒቨርስቲው ገድሉን ወደ ጥንት ቦታው መመለሱን ቤተ ክርስቲያኒቱ በከፍተኛ አድናቆት እንደምትመለከተውና እንደሚያስደስታት ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ተናግረዋል፡፡ “ጥንታዊው ብራና ቅርሳችን በመሆኑ ብንቀበለውም ስምምነቱ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን ሕጋዊ የባለቤትነት መብት የሚጎዳ፣ በትውልዱም ዘንድ የሚያስነቅፍ በመሆኑ ተቀባይነት የለውም፤” ሲሉ ተቃውመዋል፡፡
የውል ሰነዱም፣ በልዩ ጽ/ቤታቸው፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የውጭ ግንኙነት መምሪያ፣ በሕግ አገልግሎቱና በቅርሳቅርስ ጥበቃ መምሪያ በጋራ እንዲታይና እንዲመረመርም ፓትርያርኩ መመሪያ ሰጥተዋል፡፡

የደብረ ሊባኖስ ገዳም የሚገኝበትን የሰሜን ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት በሊቀ ጳጳስነት የሚመሩት አቡነ ቀውስጦስ በበኩላቸው፣ የቅርሱ መመለስ የሁላችን ደስታ ቢሆንም የተመለሰበት ሒደት ግን የቤተ ክርስቲያኗን ሥርዓትና መዋቅር እንዲሁም የገዳሙን ክብር እንዳልጠበቀ ገልጸዋል፡፡ ሦስተኛ ወገን በማስገባት በአስተዳዳሪውና በዩኒቨርስቲው የተፈረመውን ስምምነት÷ የሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት፣ ሊቀ ጳጳሱ፣ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ፣ ቅዱስ ፓትርያርኩና ቅዱስ ሲኖዶሱ ሳያውቁትና ሳይመረምሩት ሕጋዊ የባለቤትነት መብትን በሚያሳጣ መልኩ መፈጸሙን ብፁዕነታቸው አስረድተዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱን ቀኖናና መዋቅር በመጣስ “ለመታየት እና ለመግነን” ሲባል የተፈጸመው ድርጊት አግባብ ያለመሆኑን ሊቀ ጳጳሱ በርክክቡ ወቅት በመናገራቸውም፣ “እዚያች ገዳም ትኖራታለህ፤ እንተያያለን፤ የፈለከውን ሹምበት” በሚል በገዳሙ አስተዳዳሪ መዘለፋቸው ተጠቅሷል፡፡

ከዚሁ ጋር በተያያዘ የገዳሙ አስተዳዳሪ ባለፈው ረቡዕ በሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት በተጻፈ ደብዳቤ÷ ከሥራ፣ ከደመወዝና ከአገልግሎት ታግደው እንደነበር ታውቋል፡፡ ከትላንት በስቲያ የገዳሙን መነኰሳት አስከትለው በመምጣት በፓትርያርኩ ፊት ሊቀ ጳጳሱን ይቅርታ በመጠየቃቸው በመካከላቸው  ዕርቀ ሰላም ወርዷል፤ ተብሏል፡፡  ይኹንና አስተዳዳሪው “ተጠሪነቴ ለቅዱስ ፓትርያርኩ ነው” በሚል ያለሥልጣናቸው ከዩኒቨርስቲው ጋር ፈጽመውታል የተባለው ስምምነት ያስነሣቸው ስጋቶችና ተቃውሞዎች ግን መቋጫ አላገኙም፡፡

ቤተ ክርስቲያኒቱ የባለቤትነት መብቷን አሳልፋ ሰጥታ መልሳ በስጦታ መልክ የምትቀበልበት አንዳችም ምክንያት እንደሌለና የዩኒቨርስቲውም ፍላጐት እንዳልሆነ ሒደቱን በቅርበት የሚከታተሉ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡  የስጦታ ውሉ ባስነሳው ውዝግብ ሳቢያ ዩኒቨርስቲው የሕግ አማካሪውን ሳያሰናብት እንዳልቀረም እኒሁ ምንጮች ይናገራሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቷ በበኩሏ፤ “የስጦታ ውል” ሰነዱን እንደምትቃወመው ለዩኒቨርስቲው በይፋ በማሳወቅ፣ ተቀባይነት ያለው ስምምነት እንዲዘጋጅ ጥያቄ ማቅረብ እንዳለበት ተወስኗል፡፡ አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች ቤ/ክርስቲያኗ የአሜሪካንና የአውሮፓን ዩኒቨርሲቲዎች፣ ቤተ መጻሕፍትና ቤተ መዛግብት ባደመቁት  ሌሎች ቅርሶቿ አመላለስ ላይ የራሱ አዎንታዊ ተፅዕኖ ያሳድራል ብለዋል፡፡