የአማራ ፋሺዝም (ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም)

ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወርቅ መሆኑን ከተናገረ ከጥቂት ወራት በኋላ በተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ መብቶች ጉባኤ ላይ ተሳታፊ ነበርሁ፡፡ በጉባኤው ላይ ባደርገረሁት ንግግር የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ፋሺስታዊ ንግግር አደረገ ብዬ ነበር፡፡ ስወጣ የቅርብ ወዳጄ የነበረ የኢትዮጵያ አምባሳደር ተቆጥቶ እጆቹን እያወናጨፈ ‹‹አይባልም! አይባልም!›› እያለ ወደኔ መጣ፡፡ እኔም ረጋ ብዬ ‹‹አዎ አይባልም፤ ለዚህ ነው እኔም የተናገርሁት!›› ወዳጄ አምባሳደሩ የወጣለት ምሁር ነበር፡፡ ነገር ግን የፋሺስት አሽከር መሆኑ ገሀድ እንዳይወጣበት ሰግቶ ነበር፡፡

ያው አንድ ፋሺስት በቀደደው ዛሬ ብዙ ፋሺስቶች ተከትለውታል፡፡ እንዲያውም በዚህ ጉዳይ መለስ ዜናዊን የሚያስንቁ ፋሺስቶች ፈልተዋል፡፡

አንድ ምሳሌ
«የአማራ ብሄርተኝነት ለሌሎች ኢትዮጵያውያን ስጋት የማይሆንበት ተጨማሪ ምክንያት የብሄረሰቡ ትክለ ስብዕና ነው፡፡ ዐማራ የጥበብ መሃንዲስ ነው፣ ታሪክ ሰሪ፣ ድንበር አስከባሪ፣ አሰተዋይ መሪ ነው፡፡ ለአከርካሪው ሲቃጡት አናት የሚያፈርስ የጀግኖች አውራ ነው፡፡ እንደ ኢትዮጰያ አማራ የእግዜር የበኩር ልጅ ነው፡፡ በሃይማኖቱ፣ በቁርጠኛነቱ በደግነቱና በትዕግስቱ ያሰበበት ደራሽ ነው፡፡…..»

እንዲህ ያለው ባዶ ቀረርቶ ሌላ ባዶ ቀረርቶን ይጋብዛልና አይጠቅምም፡፡ የዚህ ጽሑፍ አማርኛ ቢጠና መልካም ይመስለኛል፡፡