አቶ ይልቃል ጌትነት አዲስ ፓርቲ ሲመሰርቱ ኢሕአዴግ የምክር ቤት ስብሰባውን ጀምሯል ።

የኢትዮጵያውያን አገር አቀፍ ንቅናቄ መሥራቾችና የቀድሞ ሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች እነ አቶ ይልቃል ጌትነት (ኢንጂነር)፣ ስለአዲሱ ፓርቲያቸው የምሥረታ ውይይት መጋቢት 8 ቀን 2010 ዓ.ም. አደረጉ፡፡

የምሥረታ ውይይቱ የተደረገው አፍንጮ በር በሚገኘውና የመድረክ ጽሕፈት ቤት በነበረው በኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) ጽሕፈት ቤት ሲሆን፣ ስለንቅናቄው መመሥረት አስፈላጊነት አቶ ይልቃል ለተገኙ አባላትና ተጋባዥ እንግዶች ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡

አዲስ ፓርቲ መመሥረት ያስፈለጋቸው ሌሎች ፓርቲዎችን ለመወዳደር ሳይሆን፣ ከአገዛዝ ወደ ዴሞክራሲ ለሚያደርጉት ትግል ኢትዮጵያውያንን ያካተተ አገር አቀፍ ንቅናቄ ለመፍጠር መሆኑን አቶ ይልቃል ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡

ፓርቲው ሁሉን አቀፍ የሆነና ቀደም ብሎ ከነበረባቸው ችግሮች ልምድ በመውሰድ፣ የተሻለ አደረጃጀት ለመፍጠር መሆኑንም አክለዋል፡፡ የኢትዮጵያ ችግር ብዙና ውስብስብ መሆኑን የጠቆሙት አቶ ይልቃል፣ ከችግሩ ለመላቀቅ የፖለቲካ ማሻሻያ መደረግ እንዳለበትም አስረድተዋል፡፡ በኢትዮጵያ በአሁኑ ጊዜ የተፈጠረው ፈርጀ ብዙ ውጥንቅጥ የፖለቲካና የአመራር ችግር፣ በአስቸኳይ መፈታት እንዳለበትም ጠቁመዋል፡፡

በሽብር ተግባር ወንጀል ተፈርዶባቸው የነበሩትና መንግሥት በይቅርታ የፈታቸው አቶ ዮናታን ተስፋዬና አቶ ብርሃኑ ተክለ ያሬድን ጨምሮ በርካታ ሰዎች መገኘታቸውን የገለጹት አቶ ይልቃል፣ በኢትዮጵያ ተፈጥሮ ያለውን ዘርፈ ብዙ ችግር ተባብሮና አንድ ሆኖ መፍታት ጊዜ የሚሰጠው ጉዳይ አለመሆኑን ገልጸዋል፡፡

ፓርቲው ለምሥረታ የሚያበቃውን የአባላት ቁጥር ከደቡብ፣ ከኦሮሚያና ከአማራ ክልሎች፣ እንዲሁም ከድሬዳዋና ከአዲስ አበባ ከተማ አስተደደሮች 95 በመቶ ማግኘቱን አስረድተዋል፡፡

በቤኒሻንጉል ጉምዝና በሶማሌ ክልሎችም ፊርማ ማሰባሰብ መጀመራቸውንም አክለው፣ መጋቢት 24 ቀን 2010 ዓ.ም. የምሥረታ ጉባዔ እንደሚያደርጉ አስታውቀዋል፡፡

 የ

የኢሕአዴግ ምክር ቤት ስብሰባ ከማክሰኞ መጋቢት 11 ቀን 2010 ዓ.ም. ከቀትር በኋላ መካሄድ ጀመረ፡፡

የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ከመጋቢት 2 ቀን 2010 ዓ.ም. ጀምሮ በዝግ ሲመክር መቆየቱ የሚታወስ ሲሆን፣ ስብሰባውን ሰኞ መጋቢት 10 ቀን 2010 ዓ.ም. አጠናቋል፡፡ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት ግማሽ ቀን ዕረፍት ካደረጉ በኋላ የምክር ቤቱ ስብሰባ በዝግ መካሄድ ጀምሯል፡፡

እየተካሄደ ያለው ስብሰባ ከሁለት ቀናት እንደማይበልጥ ከምንጮች ለመረዳት ተችሏል፡፡ አንድ መቶ ሰማንያ አባላት ያሉት የኢሕአዴግ ምክር ቤት፣ በዋናነት በኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ተገምግሞ በሚቀርብ ሪፖርትና ለዕይታ ይጠቅማል በተባለ ሰነድ ላይ እንደሚወያይና በመጨረሻም የድርጅቱን ሊቀመንበር እንደሚመርጥ ታውቋል፡፡

በኢሕአዴግ ብሔራዊ ድርጅቶች መካከል ያለው ውስጠ ዴሞክራሲ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየላላ እንደመጣና አገሪቱም መቋጫ ባልተገኘለት የፖለቲካ ቀውስ መቆየቷ አይዘነጋም፡፡ በአገሪቱ ከተከሰተው ቀውስ ጋር በተያያዘ አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ከፓርቲው ሊቀመንበርነትና ከአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትርነት ለመልቀቅ ጥያቄ ማቅረባቸው ይታወሳል፡፡ አቶ ኃይለ ማርያም የመልቀቂያ ጥያቄ ካቀረቡ ድፍን አንድ ወር ቢሞላቸውም፣ እስካሁን እሳቸውን የሚተካው ማን እንደሆነ አልታወቀም፡፡ የኢሕአዴግ ምክር ቤት ይህንን ክፍተት ለመሙላት ነው ስብሰባ የተቀመጠው፡፡

መንግሥት አገሪቱን በመደበኛው የሕግ ማስከበር ሥርዓት ማስተዳደር አልቻልኩም በማለቱ፣ በመላ አገሪቱ ተግባራዊ የሚሆን ለስድስት ወራት የሚቆይ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ሥራ ላይ ውሏል፡፡

አገሪቱ ካለችበት ቀውስና የሰላም መደፍረስ ሳትወጣ የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ለስምንት ቀናት በዝግ ሲመክር ቆይቷል፡፡ በስብሰባውም በአመራሩ መካከል የአመለካከት አንድነት በሚፈጠርበት፣ በአገሪቱ ሰላምና ደኅንነት በሚረጋገጥበት፣ በብሔራዊ ፓርቲዎች መካከል ጠንካራ ውስጠ ዴሞክራሲ በሚጎለብትበትና በሌሎች ጉዳዮች ላይ ሰፊ ውይይት እንዳደረገ ተገልጿል፡፡

የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው ከዚህ በፊት ፓርቲው ባስቀመጣቸው ውሳኔዎች አፈጻጸምና የታዩባቸው ጉድለቶች ሰፊ ውይይት ማድረጉን የኢሕአዴግ ጽሕፈት ቤት ባወጣው መግለጫ ጠቁሟል፡፡ ‹‹በአሁኑ ወቅት እያጋጠሙ ያሉ የአመራር ድክመቶች የወለዳቸውን ችግሮች ለማረም የሚያስችል አመለካከትና አንድነት የሚፈጥር ሁኔታ መኖሩን አረጋግጧል፤›› ሲል በመግለጫው አውስቷል፡፡

‹‹በዚህ ግምገማ የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ እያንዳንዱ ብሔራዊ ድርጅት አገሪቱ ያስመዘገባቸው ለውጦችና በሒደት ያጋጠሙ ፈተናዎች በሚመሩዋቸው ክልሎችና በአገር አቀፍ ደረጃ ያላቸውን አስተዋጽኦ በዝርዝር በመፈተሽ ጥንካሬዎቻቸው ጎልብተው እንዲቀጥሉ፣ ጉድለቶች ደግሞ በፍጥነት እንዲታረሙ አቅጣጫ አስቀምጧል፤›› ሲል በመግለጫው አስረድቷል፡፡

የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ በምክር ቤቱ አማካይነት የአመራር ክፍተቱ እንደሚሟላ ጠቁሞ ይህም በኢሕአዴግ ፕሮግራም፣ ሕገ ደንብና በተለመደው አሠራር መሠረት እንደሚሆን አስታውቋል፡፡

በሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው ስምምነት የተደረሰባቸው የውሳኔ ሐሳቦች ለኢሕአዴግ ምክር ቤት ቀርበው ተቀባይነት ካገኙ፣ የግንባሩን ሊቀመንበር ለመምረጥ ወደ ድምፅ አሰጣጥ እንደሚሸጋገር ታውቋል፡፡

ተተኪው የኢሕአዴግ ሊቀመንበር እስከ ሐሙስ መጋቢት 13 ቀን 2010 ዓ.ም. ምሽት ድረስ ይታወቃል ተብሎ እንደሚጠበቅ፣ ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ምንጮች ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡

ተተኪ የፓርቲው ሊቀመንበርና የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ማን ይሆናል? የሚለው አሁንም ድረስ የብዙዎች መነጋገርያ አጀንዳ ነው፡፡ ከተተኪው ጠቅላይ ሚኒስትር ማንነት በተጨማሪ አገሪቱን ከገባችበት ችግር ያወጣታል? የሚለውም የብዙዎች ጥያቄ ነው፡፡